አበራ ብርሃኑ ተሰማ
አበራ ብርሃኑ፣ መስከረም 1 ቀን 1928 ዓ.ም ከአባቱ ከአቶ ብርሃኑ ተሰማ ጓንጉልና ከእናቱ ከወ/ሮ አቦነሽ ጉታ አዲስ አበባ ሽሮ ሜዳ በሚባለው ሰፈር ተወለደ። እስከ 10ኛ ክፍል ተፈሪ መኮንን ት/ቤት ከተማረ በኋላ ጅማ እርሻ ት/ቤት ትምሕርቱን መከታተል ጀመረ። ጅማ እርሻ ት/ቤት በነበረበት ጊዜ በጀመረው በእርሻ ምህንድስና ትምህርት አለማያ እርሻ ኮሌጅ ገብቶ የመጀመሪያ ዲግሪውን ለማግኘት ችሏል። ከዚያም ለከፍተኛ ትምህርት ወደ ቀድሞዋ ሶቭዬት ህብረት በመሄድ በእርሻ፣ ጥጥ ተክልና ጨርቃ ጨርቅ መሣሪያዎች ምህንድስናና ምርት አገልግሎት ከፍተኛ ስልጠና በማግኘት ወደ አገሩ ተመልሷል።
ኢትዮጵያም እንደተመለሰ በጅማ እርሻ ት/ቤት በመምህርነት፣ ቀጥሎም በ1960 እና 1961 ዓ.ም. የባህር ዳር ፖሊቴክኒክ ኢንስቲትዩት ዳይሬክተር በመሆን አገልግሏል።
በዚያው ዘመን በጎጃም ክፍለ አገር ተቀስቅሶ የነበረውን የገበሬዎች አመፅ በመደገፍ ተነሳስተው የነበሩትን የፖሊ ቴክኒክ ኢንስቲትዩት ተማሪዎች ከደገፉና ካስተባብሩት አንዱ ስለነበር እስከ መታሰር፣ ከክፍለ አገሩም እስከመባረረና በወቅቱ በመንግሥት መሥሪያ ቤትም እንዳይቀጠሩ እስከመታገድ ከደረሱት መሀል አንዱ ነበር።
ለተወሰኑ ዓመታት በመንግሥትም ሆነ የግል ድርጆቶች ውስጥ የመቀጠር ዕድል ተነፍጎት ከቆየ በኋላ ጭላሎ የእርሻ ልማት ድርጅት ተቀጥሮ ከድሃ አርሶ አደር ገበሬዎች ጋር በቀጥታ በሚያገናኘው ሙያው አገሪቱንና ህዝቦቿን አገልግሏል። የኢትዮጵያ አብዮት በየካቲት ወር 1966 ከፈነዳ በኋላ ደግሞ ወደ ንግድና ኢንዲስትሪ ሚኒስቴር በመዛወር የእርሻ መሣሪያዎች ማምረቻና ማከፋፈያ ኮርፖሬሺን ዋና ሥራ አስኪያጅ በመሆን ሠርቷል።
በነሐሴ ወር 1969 ዓም መኢሶን ከደርግ ጋር የነበረውን ግንኙነት ካቋረጠ በኋላ የመኢሶንን ኅቡዕ አባሎች በመደገፍ የሚያደርገው እንቅስቀሴ ተደርሶበት በደርግ መንግሥት ታሠረ። ከአምስት ዓመት እሥር በኋላ ቢፈታም በእሥር ላይ በምርመራ ላይ በነበረበት ወቅት አስከፊ በሆነ መንገድ ስለተደበደበ በጭንቅላቱ ላይ ከፍተኛ ጉዳት ደረሰበት። ከእሥር እንደተፈታ በቂ ሕክምና እንዲያገኝ በዓለም አቀፍ ቀይ መስቀል ትብብር ወደ ስዊድን አገር ተወሰደ። ይሁንና፣ ከጽኑ ሕመሙ ሊድን አልቻለም። በዚህ አኳኋን ከ45 ዓመት የአልጋ ቁራኝነት በኋላ ጥቅምት 12 ቀን፣ 2015 ዓ.ም. ከዚህ ዓለም በሞት ተለይቷል።
አበራ ብርሃኑ፣ የሚታወቀው ላመነበት ዓላማ በፅናት በመቆም፣ በቆራጥነቱ፣ በሃቀኛነቱ፣ ቀጥተኛነቱና ገደብ የሌለው ርህራሄው ነበር። ከዚህ ሌላ አበራ በተማሪነት ዘመኑ በእጅ ኳስ፣ በዋና፣ እና በቅርጫት ኳስ ጨዋታ ችሎታው የታወቀ ነበር።
ፋሪስ ሂርጳ
ፋሪስ ሂርጳ፣ በ1939 ዓ.ም. በጨለያ ወረዳ ቶኬ ቀበሌ ተወለደ። እድሜው ለትምህርት ሲደርስ የአንደኛ ደረጃ ትምህርቱን በጌዶ ከተማ ደጃዝማች ጫጫ አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ተከታተለ። በመቀጠልም የሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱን በአምቦ ከተማ ማዕረገ ሕይወት ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ትምህርት ቤት ተከታትሎ ተመረቀ።
በትምህርቱ እጅግ ውጤታማ እና በየተለያዩ ተግባራትና ዝግጅቶች ግንባር ቀደም ሚና ይጫወት የነበረ በመሆኑ ከእድሜ አቻዎቹ አልፎ በአካባቢው ሕዝብ ዘንድ ታዋቂና ተወዳጅ ነበር። በመሆኑም፡ ክትምህርት ገበታው ተነስቶ ወደ ስራ አለም ያመራው በወቅቱ የለውጥ ጭላንጭል የሚያመላክተውን የመሬት ይዞታ ሚኒስቴርን በመቀላቀል ሆነ።
ከጊዜ በኋላም በእርሻ ሚኒስቴር የሆሮ ጉዱሩ አውራጃ ኃላፊ ሆኖ ተመደበ። በዚህ ወቅት የአርሶ አደሩን አብዮታዊ ትግል በህቡዕ ያደራጅና ይመራል ብሎ ያመነበትን መኢሶንን በአባልነት ተቀላቀለ።
በነሐሴ ወር 1969 ዓ.ም. መኢሶን የትግል ስልት ለውጥ አድርጎ አንዳንድ አባላቱን ከሕጋዊ ወደ ህቡዕ ትግል ሲያሰማራ፣ ፋሪስ ሂርጳ ከሥራ ገበታው ላይ ተይዞ ነቀምቴ የሚገኘው እጅግ አስከፊ የሆነው ጃቶ እስር ቤት ታሰረ። ከዚያም መስከረም 2 ቀን፣ 1972 ዓ.ም ከሌሎች የመኢሶን ጓዶች፣ ከብሩ ወርቁና ከእምሩ ኢብሳ ጋር በአንድነት በግፍ ተረሸነ።
ፋሪስ ከልጅነቱ ጀምሮ ለጭቁኖች መብት የቆመ፣ ለአገር እድገት አሳቢና ተከራካሪ ነበር።
እምሩ ኢብሳ
እምሩ ኢብሳ በ1931 ዓ.ም. ጅማ ገነቲ ፣ ሰላን የተባለ ቦታ ተወለደ። በቀድሞው አጠራር፣ ከቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ዩኒቨርስቲ በጂኦግራፊ ተመረቀ። ከዚያም ከታወቀው ከኬምብሪጅ ዩኒቨርስቲ በመሬት አያያዝ የድሀረ ምረቃ ዲፕሎማ አገኘ።
ትምህርቱን ከአጠናቀቀ በኋላ በተለያዩ መሥሪያ ቤቶች አገልግሏል። በመጨረሻም የሆሮ ጉዱሩ አውራጃ አስተዳዳሪ ሆኖ ሠርቷል። አውራጃ አስተዳዳሪ በነበረበት ወቅት በሕዝብ ዘንድ ተወዳጅ ከመሆኑ ሌላ፣ በ1967 ዓ.ም. የታወጀው የገጠር የመሬት አዋጅ በሥራ ላይ እንዲውል በአካባቢው ከነበሩ ገበሬዎች፣ ተማሪዎችና ተራማጅ ኃይሎች ጋር ተባብሮ በመሥራት ይታወቅ ነበር።
መኢሶን በ1969 ዓ.ም. ነሓሴ አጋማሽ ላይ የትግል ስልት ለውጥ ሲያደርግ፣ እምሩ በደርግ መንግሥት ተወካይ በነበረው ንጉሴ በሚባል የደርግ አባል ትዕዛዝ ታሰረ። እጀግ አስከፊ በሆነው በነቀምቴ ጃቶ እስር ቤት ሲንገላታና ሲሰቃይ ከከረመ በኋላ መስከረም 2 ቀን፣ 1972 ዓ.ም ከሌሎች የመኢሶን ጓዶች፣ ከብሩ ወርቁና ክፋሪስ ሂርጳ ጋር በአንድነት በግፍ ተረሸነ።
ብሩ ወርቁ
ብሩ ወርቁ ወለጋ ክፍለ አገር በሆሮ አውራጃ፣ አካጂ ቀበሌ ገረን ኮንሶ በሚባል ቦታ ከአባቱ ከአቶ ወርቁ ቂጤሳና ከ እናቱ ወ/ሮ ቱርቱ ዲንሳ በ1934 ዓ.ም. ተወለደ። የአንደኛና ሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱን ከአጠናቀቀ በኋላ ሐረር መምህራን ማሰልጠኛ ተቋም ገብቶ ትምህርቱን አጠናቀቀ። ከዚያም በወለጋ አርጆ መኮና፣ አኖ በመምህርነት አገልግሏል።
ለጥቂት አመታት በመምህርነት ከአገለገለ በኋላ፣ በ1963 ዓ.ም. ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ዩኒቨርስቲ ገባ። ወቅቱ የተማሪዎች ማኅበር ሊቀመንበር የነበረው ጥላሁን ግዛው የተገደለበት ጊዜ ነበር። ብሩም በጊዜው ተጋግሎ በተነሳው የተማሪዎች የተቃውሞ እንቅስቃሴ ውስጥ በንቃት ተሳትፏል። በዚያው ዓመትም ትምህርቱን ለማቋረጥ ስለተገደደ፣ በወለጋ ሻምቡ በአቤ ደንጎሮ ት/ቤት በመምህርነት ተቀጥሮ መሥራት ጀመረ። ከዚያም በመቀጠል አዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ተመልሶ ትምህርቱን ሲከታተል ከቆየ በኋላ በ1967 ዓ.ም. በእድገት በህብረት ዘመቻ ተሳትፏል።
በኢትዮጵያ ገጠር፣ መሬትን ለአራሹ ያደረገውን አዋጅ በሥራ ላይ ለማዋል በተደረገው እንቅስቃሴም፣ ብሩ ወርቁ የመሬታ ይዞታ ሚኒስቴር ተጠሪ በመሆን በሊሙ ወረዳና በሆሮ አውራጃዎች ገበሬዎችን በማደራጀትና አዋጁን ሥራ ላይ በማዋል ከፍተኛ አስተዋጽኦ አድርጓል።
ብሩ ሕይወቱን ለኢትዮጵያ ሕዝብ የሰዋ ታጋይ የመኢሶን አባል ነበር። ኅዳር 13፣ 1970 ዓ.ም. መደበኛ ሥራውን በማኪያሄድ ላይ እያለ በደርግ ወታደሮች ተይዞ ሁለት ዓመታት በእስር ቤት ተሰቃየ። ከአካል ድብደባና ስቃይ በኋላ፣ እርሱንና ሁለት ጓዶቹን – እምሩ ኢብሳንና ፋሪስ ሂርጳን – ደርግ ከእስር ቤት አውጥቶ ገደላቸው።
ንግሥት አዳነ (ዶ/ር)
ዶክተር ንግሥት አዳነ ነሐሴ 1937 ዓ.ም. ሓረቆ፣ ትግራይ ተወለደች። አንደኛ ደረጃ ትምህርቷን መቀሌ አፄ ዮሐንስ ት/ቤትና ሲዳሞ፣ ይርጋዓለም ራስ ደስታ ዳምጠው ት/ቤት ተከታተለች። ሁለተኛ ደረጃ ተምህርቷን ደግሞ በአዲስ አበባ እቴጌ መነን ት/ቤት አጠናቀቀች። ንግሥት ከክፍሏ ሁልጊዜ አንደኛ ትወጣ የነበረች ጎበዝ ተማሪ ነበረች። የሁለተኛ ደረጃ ትምህርቷን ከጨረሰች በኋላ በዚያን ጊዜ ሶቪየት ህብረት ተብላ በምትታወቀው ሩሲያ በሕክምና ሙያ በዶክትሬት ዲግሪ ተመርቃለች።
ሩሲያ በነበረችበት ጊዜያት በአውሮፓ የኢትዮጵያ ተማሪዎች ማኅበር የነቃ ፖለቲካዊ ተሳትፎ ነበራት። ኢትዮጵያ ከተመለሰች በኋላ ስፔሻላይዝ በአደረገችበት የሕጻናት ሕክምና ሙያዋ አገልግላለች።
ንግሥት ከ1968 ዓ.ም. አጋማሽ ጀምሮ የሕዝብ ድርጀት ጊዜያዊ ጽ/ቤት አባል፣ እንዲሁም የካቲት 66 የፖለቲካ ት/ቤት መምህር ሆናም ሠርታለች። የመኢሶን ጠቅላይ ኮሚቴ አባልና የመኢሶን የሴቶች ክንፍ፣ የኢትዮጵያ ሴቶች አብዮታዊ ንቅናቄ (ኢሴአን) መሥራችና መሪም ነበረች።
በ1968 ዓ.ም. ዶክተር ንግሥት ‘ሴቶችና የሕብረተሰብ እድገት’ በሚል ርዕስ በተለያዩ የህብረተሰብ ሥርዓቶች ውስጥ ሴቶች ላይ የሚደርሰውን ጭቆና የሚተነትን ጥናታዊ መጽሐፍ ለንባብ አብቅታለች።
መኢሶን የትግል ስልት ለውጥ አድርጎ በኅቡዕ መንቀሳቀስ ሲጀምር፣ በኅቡዕ በተሠማራችበት በሃዲያ አውራጃ በደርግ ወታደሮች ተይዛ ታሰረች። ከዚያም ሐምሌ 5 ቀን 1971 ዓ.ም. ደርግ ንግሥትን ከታሰረችበት እስር ቤት አውጥቶ ከኃይሌ ፊዳ፣ ሃይሉ ገርባባ፣ ቆንጂት ከበደና ከባለቤቷ ከደስታ ታደሰ ጋር ያለ ምንም ፍርድ በድብቅ ገደላት።
ንግሥት ከሰው ጋር ተግባቢና ለሰዎች ደህንነት የምትጨነቅ ነበረች። እንዲሁም እጀግ የተወሳሰበ ሁኔታን ቀለል ባለ መልክ አስረድታ ሰውን ማሳመን የምትችልና በአካባቢዋ ያሉትን ሁሉ የምታስተባብርና የምትመራ ጓድ ነበረች።
የደርግ መንገስት በወደቀ በሁለተኛ አመት፣ የዶ/ር ንግሥት አጽም በሚስጥር ተገድላ ከተቀበረችበት ከራስ አስራተ ካሳ ግቢ ወጥቶ በቤተሰቧ መካነ መቃብር በክብር አርፏል።
ዶክተር ንግሥት አዳነ አብሯት በደርግ የተገደለው የደስታ ታደሰ ባለቤትና የሰባት ዓመት ልጅ እናት ነበረች።
ቆንጂት ከበደ
ቆንጂት ከበደ፣ የካቲት 30፣ 1945 ዓ.ም. ከእናቷ ከወ/ሮ አሰለፈች ዳርጌና ከአባቷ ከደጃዝማች ከበደ ይርዳው አዲስ አበባ ተወለደች። የአንደኛና ሁለተኛ ደረጃ ትምህርቷን በሊሴ ገብረ ማርያም ት/ቤት ከአጠናቀቀች በኋላ በፈረንሳይ አገር ከኤክስ-አን- ፕሮቫንስ ዩኒቨርስቲ በሳይኮሎጂ የመጀመሪያ ዲግሪዋን በማግኘት ተመርቃለች።
ቆንጂት፣ በአውሮፓ ተማሪዎች ማህበርና በመኢሶን ውስጥ ሕዝብ በማንቃትና በማደራጀት እንቅስቃሴ ከፍተኛ ተሳትፎ ነበራት። በተለይም መኢሶን ውስጥ በተለያዩ የድርጅቱ የትግል እንቅስቃሴዎች ከፍተኛ አስተዋጽኦ የነበራት፣ ሙሉ ጊዜዋን ለአብዮቱ የሰዋች ታጋይ ነበረች። የመኢሶን የሴቶች ክንፍ የሆነው የኢትዮጵያ ሴቶች አብዮታዊ ንቅናቄ (ኢሴአን) አመራር አባልም ሆና አገልግላለች።
ቆንጂት፣ መኢሶን በነሐሴ ወር አጋማሽ 1969 ጅምሮ በኅቡዕ ትግሉን ለመቀጠል ከወሰነ በኋላ የተሰጣትን ተግባራት ስታከናውን፣ አዲስ አበባ ተክለ ሃይማኖት አካባቢ በደርግ ወታደሮች ተይዛ ታሰረች።
ሁለት ዓመት ያህል በእስር ላይ ከቆየች በኋላ፣ ሐምሌ 5 ቀን 1971 ዓ.ም. ከታሰረችበት እስር ቤት ተወስዳ ከኃይሌ ፊዳ፣ ደስታ ታደሰ፣ ኃይሉ ገርባባና ዶ/ር ንግሥት አዳነ ጋር ያለ ምንም ፍርድ በደርግ በድብቅ ተገደለች። እንደ ዶ/ር ንግሥት፤ የሷም አጽም በሚስጥር ተገድላ ከተቀበረችበት ከራስ አስራተ ካሳ ግቢ ወጥቶ በቤተሰቧ መካነ መቃብር በክብር አርፏል።
ቆንጂት ሕይወቷ ሲያልፍ የ26 ዓመት ወጣት ነበረች።
ኃይሉ ገርባባ
ኃይሉ ገርባባ፣ ወለጋ ክፍለ አገር ከአባቱ ከአቶ ገርባባ ጋጋ እና ከእናቱ ከወ/ሮ አስቻለች ፋንታ በሆሮ ጉድሩ አውራጃ ጂማ ገነቴ ከተማ ተወለደ። የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርቱን በሻምቡ ከተማ ከተከታተለ በኋላ አዲስ አበባ በሚገኘው የንግድ ሥራ ትምህርት ቤት ትምህርቱን አጠናቆ በዲፕሎማ ተመረቀ። በመቀጠልም ለጥቂት ጊዜ በባኮ የእርሻ ምርመር ተቋም ውስጥ ካገለገለ በኋላ ለከፍተኛ ትምህርት አዲስ አበባ ዩኒቨርሲት ገባ። በፖለቲካል ሳይንስ ክፍል ትምህርቱን በመከታተል ላይ ሳለ በዩኒቨርስቲ ተማሪዎች ውስጥ በነበረው ንቁ የፖለቲካ ተሳትፎ ሳቢያ ወደ ሱዳን ለመሰደድ ተገደደ።
በሱዳን ቆይታውም ካርቱም ዩኒቨርሲቲ በመግባት በፖለቲካል ሳይንስ በዲግሪ ተመረቀ። ከትምህርቱም ባሻገር ምስጢር በሆነ ድርጅታዊ ተልእኮ ሱዳን ሄዶ ካርቱም ዩኒቨርሲቲ በማስተማር ሥራ ላይ ይገኝ ከነበረው የመኢሶን መሥራች አባል ከነበረው ከዶ/ር ከድር መሐመድ ጋር በቅርብ እየተገናኘ በኅቡዕ ሲንቀሳቀስ ቆየ።
የየካቲት 1966 ሕዝባዊ አብዮትን ተከትሎ በ1967 ዓ.ም. መጀመሪያ ላይ ከካርቱም ወደ አገሩ በመመለስ መኢሶን የሰጠውን ተልእኮ በመፈጸም ላይ ቆይቶ በ1968 ዓ.ም. በወለጋ ክፍለ አገር የሕዝብ ድርጅት ጉዳይ ጊዜያዊ ጽ/ቤት ኃላፊ በመሆን ከምክትል ባልደረባው ከካሳሁን ብርሃኑ ጋር ሆኖ እስከ ነሐሴ 1969 ዓ.ም. አርሶ አደሮችን፣ ወዛደሮችን፣ የቢሮ ሠራተኞችን፣ መምህራንን እና ወጣት ተማሪዎችን በማደራጀትና በትግሉ በማሳተፍ ከፍተኛ አስተዋጽኦ አድርጓል።
መኢሶን በደርግ ላይ የነበረውን ሂሳዊ ድጋፍ ሲያነሳ ኃይሉ ገርባባ በነሐሴ 1969 ዓ.ም. ወደ ገጠር ወለጋ ከጓዶቹ ጋር ለትግል ተሠማራ። በገጠር እያለ በደርግ መንግሥት ወታደሮች ተይዞ ታሠረ። በመጀመሪያ ወደ ነቀምቴ እስር ቤት ከዚያም ወደ አዲስ አበባ ከተወሰደ በኋላ፣ አራተኛ ክፍለ ጦር እስር ቤት ከሌሎች የመኢሶን ጓዶቹ ጋር በእስር ላይ ቆየ።
ከታሠረ ከሁለት ዓመት በኋላ፣ ሐምሌ 5 ቀን 1971 ዓ.ም. ከሌሎች የመኢሶን ጓዶቹ ከኃይሌ ፊዳና ከደስታ ታደሰ ጋር ከታሰረበት ከአራተኛ ክፍለ ጦር እስርቤት፣ እንዲሁም ከርቸሌ ታስረው ከነበሩት ከዶ/ር ንግሥት አዳነና ከቆንጂት ከበደ ጋር ተወስዶ በድብቅ ያለምንም ፍርድ በግፍ ተገደለ። ተገደሎ የተቀበረበት ሥፍራም እስካሁን ድረስ አልታወቀም።
ኃይሉ ገርባባ፣ በታጋይነቱና በቆራጥነቱ፣ እንዲሁም ጌረርሳ ተብሎ በሚታወቀው ሃሳብን የመገለጽና ቀስቃሽ በሆነው በአፋን ኦሮሞ ቋንቋ የቀረርቶ ክህሎት ልዩ ተሰጥኦ እንደነበረው በቅርብ የሚያውቁት ብዙዎች ይመሰክሩለታል።
ደስታ ታደሰ
ደስታ ታደሰ፣ ከእናቱ ከወ/ሮ ፋንታዬ ሩፋኤል እና ከአባቱ ከፊታውራሪ ታደሰ ማርቆስ በአዲስ አበባ ከተማ በ1935 ዓ.ም. ተወለደ። ደስታ የአንደኛ እና የሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱን የተከታተለው አዲስ አበባ በሚገኙት የጄኔራል ዊንጌት እና የቅዱስ ዮሴፍ ትምህርት ቤቶች ነው። ደስታ የሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱን በቅዱስ ዮሴፍ ትምህርት ቤት ካጠናቀቀ በኋላ ለጥቂት ዓመታት በኢትዮጵያ ቱሪስት ድርጅት እና በኢትዮጵያ የሞስኮ ራዲዮ የአማርኛ ዝግጅት ክፍል አገልግሏል። ከዚያም ለከፍተኛ ትምህርት ወደ ቀድሞዋ ሶቭየት ህብረት አቀና።
በሶቨየት ህብረት ቆይታውም ከፍተኛ ትምህርቱን የተከታተለው በሲኒማቶግራፊ የትምህርት ዘርፍ ነበር። ከትምህርቱ በተጓዳኝም በሞስኮ ራዲዮ የአማርኛው ክፍል ባልደረባ በመሆንም አገልግሏል። ደስታ፣ በነበረበት በሶቭየት ህብረትም ሆነ በአውሮጳ የኢትዮጵያ ተማሪዎች ማኅበር ንቁ ተሳትፎ ከሚያደርጉትና አመራር ከሚሰጡት መሀል አንዱ ነበር። በሶቭየት ህብረት ቆይታው በአውሮጳ የተማሪዎች እንቅስቃሴ ውስጥ ንቁ ተሳትፎ ከነበራት እና ትምህርቷን በከፍተኛ ሕክምና ዘርፍ ከተከታተለችው ከዶክተር ንግሥት አዳነ ጋር ትዳር መስርተው አንድ ወንድ ልጅ አፍርተዋል።
በ1966 ዓ.ም. የለውጥ ማዕበል ሀገራችንን ሲጎበኝ ደስታ እና ባለቤቱ ዶ/ር ንግሥት አዳነ የጥቂት ዓመታት እድሜ የነበረውን ልጃቸውን ይዘው ለለውጡ የበኩላቸውን አስተዋጽኦ ለማድረግ ወደ አገራቸው ተመለሱ። ከተመለሱም በኋላ አባል የነበሩበት ድርጅታቸው መኢሶን የሰጣቸውን የማንቃት እና የማደራጀት ተልእኮ በትጋት ይወጡ ጀመር። ደስታ፣ ከፖለቲካ ተሳትፎው በተጨማሪ ከታወቀው የፊልም ዳይሬክተር ሚሼል ፓፓታኪስ ጋር በመሆን የኢትዮጵያ ፊልም ማዕከልን አቋቁሟል።
ደስታ በአማርኛ፣ በእንግሊዘኛ፣ በፈረንሳይኛ እና በራሽያን ቋንቋዎች ልዩ ተሰጥኦ እና ክህሎት ነበረው። በማኅበራዊ ሕይወቱም ከሰው ጋር በቀላሉ ተግባቢ እና ተጫዋች ነበር። የቅርብ ወዳጆቹ፣ ደስታ ሁሉን ሰው በእኩል ዓይን የማየት የማክበርና የመንከባከብ ባህሪ የነበረው፣ አዲስ የተዋወቁትን ሰዎች በአጭር ጊዜ መማረክና ወዳጅ ማድረግ የሚችል፣ ቁም ነገረኛና ጥሩ አድማጭ ነበር በማለት ያስታውሱታል።
መኢሶን ከደርግ ጋር ሂሳዊ ድጋፍ በሚለው መርሆ በተወሰነ ደረጃ ትብብር ሲጀምር ደስታ በባህል ሚኒስቴር ቋሚ ተጠሪ በመሆን ተመድቦ ድርጅቱ ትብብሩን አቋርጦ ኅቡዕ እስከገባበት እስከ ነሐሴ 1969 ዓ.ም. በዚሁ ደረጃ ሲያገለግል ቆይቷል። ከጥቂት ጊዜ በኋላም ኅቡዕ ገብቶ በነበረበት በከምባታ እና ሃዲያ አውራጃ ባለቤቱን ዶ/ር ንግሥትን ጨምሮ ከሌሎች የመኢሶን ጓዶች ጋር በደርግ ወታደሮች እጅ ወደቀ። በደርግ የምርመራ ክፍል ብዙ እንግልት ከደረሰበት በኋላ አራተኛ ክፍለ ጦር ግቢ ውስጥ ወደ ነበረው እስር ቤት ተዛወረ።
ከዚያም ከሌሎች የመኢሶን ጓዶች ጋር በእስር ከቆየ በኋላ ሐምሌ 5 ቀን 1971 ዓ.ም. ከኃይሌ ፊዳ እና ከኃይሉ ገርባባ ጋር ከታሰረበት ከአራተኛ ክፍለ ጦር ግቢ ተወስደ። በዚያኑ ቀን ወህኒ ቤት የነበሩት ባለቤቱ ዶክተር ንግሥት አዳነ እና ወ/ት ቆንጂት ከበደ ተጨምረው ሁሉም በአንድነት በድብቅ በግፍ ተገደሉ።
ደስታ ሕይወቱ የተቀጠፈው በ36 ዓመቱ ነበር።
ኃይሌ ፊዳ
ኃይሌ ፊዳ፣ ከአባቱ ከአቶ ፊዳ ኩማ እና ከእናቱ ከወ/ሮ ጉዲኒ ደጋ በወለጋ ክፍለ አገር በአርጆ ከተማ በ1932 ዓ.ም. ተወለደ። የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርቱን በተወለደባት በአርጆ ከተማ እና በነቀምቴ ከተማ ተከታተለ። የሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱን የተከታተለው አዲስ አበባ በሚገኘው የጄነራል ዊንጌት አዳሪ ትምህርት ቤት በነጻ የመማር ዕድል አግኝቶ ነው። አብረውት የነበሩ ተማሪዎች በጎበዝ ተማሪነቱ ያስታውሱታል። የሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱንም ያጠናቀቀው በከፍተኛ ማዕረግ ነበር።
በ1952 ዓ.ም. የሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱን አጠናቆ አንድ ዓመት በሐረርጌ ክፍለ አገር በደደር ከተማ በመምህርነት ካገለገለ በኋላ፣ በወቅቱ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ኮሌጅ በኋላም ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ዩኒቨርስቲ በመባል ይታወቅ በነበረው የትምህርት ተቋም ገብቶ በ1955 ዓ.ም. የባችለር ኦፍ ሳይንስ ዲግሪውን በጂኦሎጂ እና ፊዚክስ በከፍተኛ ማዕረግ ተቀበለ። በዩኒቨርሲቲ ቆይታውም ኃይሌ የፖለቲካና ማኅበራዊ ለውጥ ይጠይቅ በነበረው የተማሪዎች እንቅስቃሴ በንቃት ይሳተፍ ነበር። የቅርብ ጓደኞቹ እንደሚመሰክሩት በዚህን ወቅት ነበር በሶሻሊስት ርዕዮተዓለም እየተመሰጠ መሄድ የጀመረው። ከዩኒቨርሲቲው ሲመረቅ ባገኘው ከፍተኛ ውጤትም እዚያው ረዳት መምህር እንዲሆን ተመርጦ ማስተማር ቀጠለ።
በ1956 ዓ.ም. አንድ ዓመት በረዳት መምህርነት ካገለገለ በኋላ የድህረ ምረቃ ትምህርቱን ለመከታተል ነጻ የትምህርት ዕድል አግኝቶ የጂኦሎጂ ትምህርቱን ፈረንሳይ፣ ፓሪስ ተከታትሏል። በተጨማሪም በእውቁ የሶርቦን ዩኒቨርሲቲ የድህረ ምረቃ ትምህርቱን ተከታትሎ በሶስዮሎጂ በማስተርስ ዲግሪ ተመርቋል። በፈርንሳይ በኤኮል ናሲዮናል ዴ ላንግ ኦርዬንታል ቪቫንት እንዲሁም ጀርመን በሀምቡርግ ዩኒቨርስቲ አስተምሯል።
በፈረንሳይ አገር ቆይታውም ኃይሌ ፊዳ በአውሮጳ የኢትዮጵያ ተማሪዎች ማህበርን በማደራጀት እና በማንቃት ግንባር ቀደም ተሳትፎ በማድረግ ይታወቃል። ኃይሌ በኅብረተሰብ እድገት፣ ፍልስፍና፣ ቋንቋ፣ በኢትዮጵያ የፖለቲካና ኤኮኖሚያዊ ሁኔታዎች፣ ማኅበራዊ ጉዳዮች እና በሌሎች በርካታና አብይ ርእሶች ላይ ጽሁፎችን በተለያዩ ቋንቋዎች አዘጋጅቶ አበርክቷል። “ታጠቅ” እና “ትግላችን” ይባሉ በነበሩት በአውሮጳ የኢትዮጵያ ተማሪዎች ማህበር መጽሄቶች ላይ በተለያዩ የብዕር ስሞች በሚያቀርባቸው ጥልቅ ሃሳብ አዘልና ግልጽ መጣጥፎቹ፣ በስብሰባዎች ላይ በሚሰነዝራቸው ጠለቅ ያሉ ገንቢ ሃሳቦቹ ይታወቃል።
በነሐሴ ወር 1960 ዓ.ም. ምዕራብ ጀርመን፣ በሀምቡርግ ከተማ የመላው ኢትዮጵያ ሶሻሊስት ንቅናቄ (መኢሶን) ሲመሠረት ከመሥራች አባላቱና መሪዎች መሃል አንዱ ነበር። የመኢሶን ጠቅላይ ኮሚቴ የመጀመሪያው ዋና ጸሓፊ በመሆንም ተመርጦ በመሪነት አገልግሏል። ወደ ኢትዮጵያ ከተመለሰበት ጊዜ ጀምሮም የመኢሶን ልሳን የነበረው ‘የሰፊው ሕዝብ ድምፅ‘ ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ ሆኖ ሠርቷል።
ኃይሌ፣ የቋንቋ ዝንባሌ እና ተሰጥኦም ነበረው። አፋን ኦሮሞ፣ አማርኛ፣ እንግሊዘኛ፣ ፈርንሳይኛ እና ጀርመንኛን አቀላጥፎ ይናገር ነበር። ከእነዚህም በተጨማሪ በእስር ቆይታው ቀደም ብሎ ጀምሮት የነበረውን የአረብኛ እና የትግርኛ እውቀቱን የላቀ ደረጃ አድርሶት ነበር። የሩስያን ቋንቋም በመማር ላይ ሳለ ነበር ሕይወቱ የተቀጠፈችው።
ኃይሌ ለአፋን ኦሮሞ መዳበር ፈደሉን ከመቅረጽ አንስቶ፣ የሰዋስው መጽሐፍ በማዘጋጀት ከፍተኛ አሰተዋጽኦ አድርጓል። ቋንቋውንም በፈረንሳይ አገር በቅርብ ምሥራቅ ቋንቋዎች ኢንስቲትዩት እና በጀርመን አገር በሀምቡርግ ዩኒቨርሲቲ በመምህርነት በማገልገል አስተዋውቋል። ከቋንቋ አስደናቂ ተሰጥኦው በተጨማሪም ሰዕል የመሳል እና የተለያዩ ሙዚቃዎችን አዳምጦ የማድነቅና የመረዳት ችሎታም ነበረው።
የየካቲት 1966 የኢትዮጵያ ሕዝባዊ አብዮት መቀጣጠሉን ተከትሎ ኃይሌ የበኩሉን የትግል ድርሻ ለማበርከት በጥር 1967 ዓ.ም. ወደ አገር ቤት ተመለሰ። እንደተመለሰም ጥቂት ቀደም ብሎ በመኢሶን የተቋቋመውን ተራማጅ የመጻሐፍት መደብር በአስተዳዳሪነት መርቷል። እንዲሁም፣ ‘ዲያሌክቲካዊና የታሪክ ቁስአካልነት’ በሚል ርእስ በ1968 ዓ.ም. ያሳተመውና በአዲስ ዘመን ጋዜጣ ላይ እጅግ የተጋጋለ ውይይት የቀሰቀሰው መፅሐፉ የማርክሲዝም ፍልስፍና ጽንሰ-ሃሳብ በሰፊው እንዲታወቅ አስተዋጻኦ አድርጓል።
መኢሶን በደርግ መንግሥት ላይ ሂሳዊ ድጋፍ የሚለውን አቋም መውሰዱን ተከትሎ የሕዝብ ድርጅት ጉዳይ ጊዜያዊ ጽ/ቤት ሲመሠረት፣ ጽ/ቤቱን በሊቀ መንበርነት መርቷል። በጽ/ቤቱ አማካኝነት የወጣውን የብሔራዊ ዴሞክራሲያዊ አብዮት ፕሮግራምን በማርቀቅም ቁልፍ ሚና ነበረው። ከዚሁ ጋር በተጓዳኝ እንዲወጣ ታስቦ የነበረውን፣ ነገር ግን ደርግ በሕግ ለማጽደቅ ፈቃደኛ ያለሆነበትን የዴሞክራሲያዊ መብቶች አዋጅ በማርቀቅ እና ረቂቁ ጸድቆ እንዲዋጣ ብዙ ታግሎ ነበር።
በተጨማሪም፣ ኃይሌ ብዙ ጥረት አድርጎበት የነበረው ጉዳይ በወቅቱ የብዙ ኢትዮጵያንን ሕይወት እየቀጠፈ እና ንብረት እያወደመ ለረጅም ጊዜ የቆየውን የኤርትራ ጦርነት ጉዳይ በድርድርና በሰላም የሚቋጭበትን መንገድ መሻት ነበር። ለዚህም ዓላማ፣ በደርግ መንግሥትና በኤርትራ አማጺያን ግንባሮች መካከል ውይይት እንዲጀመር፣ ኤርትራ ድረስ ከሰላም ልዑካን ጋር በመጓዝ ለሰላም ድርድርና እርቅ ከፍተኛ ጥረት አድርጓል።
መኢሶን በደርግ መንግሥት ላይ የነበረውን ሂሳዊ ድጋፍ የሚለውን የፖለቲካ አቋሙን አንስቶ በነሐሴ 1969 ኅቡዕ ገባ። በዚህም ምክንያት፣ ኃይሌም ከጥቂት የመኢሶን ጓዶችና አመራር አባሎች ጋር ከከተማ ሳይርቅ የገጠሩና የከተማውን ትግል ለማቀነባበር የሚመችና አስተማማኝ ተብሎ የተገመተው የሙሎ ወረዳ ውስጥ ሆኖ እንዲታገል ተወሰነ። ሆኖም፣ በጳጉሜ 2 ቀን 1969 ዓ.ም. ኃይሌ በደርግ መንግሥት ወታደሮች እጅ ወደቀ።
በእስር ላይ እያለም፣ በደርግ ጽ/ቤት የምርመራ ክፍል ብዙ እንግልትና ድብደባ ተፈጸመበት። ከዚያም በ4ኛ ክፍለ ጦር ግቢ ውስጥ ወደነበረው የደርግ እስር ቤት አዛውረውት ለሁለት ዓመታት እስከ ሐምሌ 1971 ዓ.ም. ካቆዩት በኋላ፣ ከደስታ ታደሰ፣ ሃይሉ ገርባባ፣ ዶ/ር ንግሥት አዳነና ቆንጂት ከበደ ጋር በድብቅ በግፍ ተገደለ።
በቅርብ የሚያውቁት ሁሉ ኃይሌ በጥልቅ እውቀቱ፣ በአስተዋይነቱ፣ በአድማጭነቱ፣ በእርጋታው፣ በትህትናው እና ለተበደለ ሁሉ በተቆርቋሪነቱ ያስታውሱታል።
ኃይሌ ፊዳ፣ ከትዳር አጋሩ ከበርናዴት ኃይሌ ፊዳ ሁለት ሴት ልጆችን አፍርቷል።
